2016 ኦክቶበር 19, ረቡዕ

አብረሃ ወ አጽበሃ

Ethiopia shall soon stretch out her hands unto God.
ABRAHA WE-ATSBAHA  
ግማሽ አካሉን ከምድር ውስጥ የሸሸገ አስገራሚ መስህብ ነው፡፡ ከአለት ተጠርቦ የተሰራው እና ከተፈለፈለበት አብይ አለት ጋር ሳይላቀቅ የቆመው ቅርስ ያፈዛል፡፡ ያላየው አይፈዝምና እንዴት አትበሉኝ፤ ከዐለቱ የመስቀል ቅርጽ ያለው ህንጻ ቤተ ክርስቲያን፤ ስፋቱ 16 ሜትር በ13 ሜትር ነው፡፡
የጣሪያው ቁመት ሰባት ሜትር ይደርሳል፡፡ 13 የሚሆኑት ጣሪያውን ደግፈው የቆሙት አምዶች ግዙፍና ድንቅ ናቸው፡፡ በሐረግ ሥነ-ጥበብ ያጌጠው ጣሪያ ቀና ብሎ ለሚመለከተው ሰው አድናቆትን ያጭራል፡፡
ቄሰ ገበዙ መጡ፤ ሰላምታ ተለዋወጥን፤ አማርኛ እየቸገራቸው ጉዳዬን ነገርኳቸው፡፡ ከፈቱልኝ፡፡ አብረውኝ ያሉትን ይበልጥ በማመን እንደከፈቱልኝ ገብቶኛል፡፡
ውስጡ ደግሞ ልዩ ነው፡፡ ሶስት አብያተ መቅደሶች አሉት፤ ቀኙ የቅዱስ ሚካኤል ግራው የቅዱስ ገብርኤልና መካከሉ ደግሞ የቅድስት ማርያም ታቦተ መንበሮች አሉበት፡፡ አስደናቂው ውቅር ውስጣዊ ውበቱ ከተሰራበት ዘመን ጋር ሲነጻጸር ተአምር ነው፡፡ በአንዳንድ የውጪ ጸሐፍት ዘንድ በትግራይ ካሉ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ የሚበልጥ እንደሆነ ተገምቷል፡፡
በውቅሩ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተሳሉት መንፈሳዊ ስዕሎች በ17ኛው ክፍለ ዘመን የተሰሩ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ጥንታዊና እና እጹብ የሥነ ሥእል ውጤቶች መካከል የአባ ሰላማ ፍሬምናጦስ ስእል ይገኝበታል፡፡ በተመሳሳይ በቅኔ ማህሌቱ የሚታዩት ስእሎችም የጻድቃን፣ የመላእክትና የሰማእታትን ገድሎች ያሳያሉ፡፡
አንዳንዶች የተሰራበት ዘመን ላይ የተለያየ አመለካከት ቢኖራቸውም፤ የደብሩ አስጎብኚ ግን በ4ኛው ክፍለ ዘመን የተሰራ እንደሆነ ከእርግጠኝነት አልፈው ነገሩኝ፡፡ የሳቸውን ማመን ይሻላል፡፡
ስላየሁት ልንገራችሁ የአባ ሰላማ መስቀል፣ ደግሞ የአብረሃ ወ አጽበሃ የወርቅ ጫማን፣ ወንበራቸውን…..እንዴት የታደለ ስፍራ ነው፡፡

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ